top of page

የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ

“ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ

ይጨመርላችኋል።” (ማቴ. 6:33)

ባለፈው ሳምንት ማየት እንደጀመርነው የእግዚአብሔር ቃል አስቀድመን መፈለግ ያለብንን

ነገር ያስተምረናል። በቃሉ መሰረት አስቀድመን መፈለግ ያለብን የእግዚአብሔርን መንግስትና

የእግዚአብሔርን ጽድቅ ነው። “አስቀድማችሁ” የሚለው ቃል ለክሪኩ “proton” ለሚለው ቃል

የተሰጠ ፍቺ ነው። በመጽሐፍ ቅዱሳችን “ፕሮቶን” በጊዜ፣ በደረጃ፣ በቁጥር፣ በሚሰጠው ጥቅም

የመጀመሪያና ቀዳሚ የሆነ ጉዳይን የሚያመልክት ነው። “ፕሮቶን” ዋና ተፈላጊ ጉዳይን፣ በጣም

ጠቃሚ የሆነ ጉዳይን ያመለክታል። ለምሳሌ መጽሐፍ ቅዱሳችን ስለ አምልኮ ሲናገር “እንግዲህ

መባህን በመሠዊያው ላይ ብታቀርብ፥ በዚያም ወንድምህ አንዳች በአንተ ላይ እንዳለው ብታስብ፥

በዚያ በመሠዊያው ፊት መባህን ትተህ ሂድ፥ አስቀድመህም ከወንድምህ ጋር ታረቅ፥ በኋላም

መጥተህ መባህን አቅርብ” ይለናል (ማቴ. 5፡ 23-24)። በዚህ አግባብ መሰረት ከአምልኮ በፊት

ምቅደም—“ፕሮቶን” መሆን ያለበት ጉዳይ ወይንም እግዚአብሔር ቀዳሚ አድርጎ የሚያየው ጉዳይ

ከወንድማችን ከእህታችን ጋር ያለን ስምምነት፣ እርቅና ሕብረት ነው። ከወንድማችን ጋር ተጣልተን

እግዚአብሔርን በእውነት ማምለክ እንችልም። ስለዚህ ከአምልኮ በፊት እርቅ ዋና ነገር ነው ማለት

ነው። በሌላ ምሳሌ ደግም መጽሐፍ ቅዱስ መቅደም ስላለበት ነገር ሲያስተምረን በሌላው አይን

ውስጥ ያለውን ጉድፍ ከማውጣታችን በፊት አስቀድመን በአይናችን ውስጥ ያለውን ምሶሶ

እንድናወጣ ይመክረናል። (ማቴ 7:5)

ከላይ ባሰፈርነው ክፍል ደግም ቃሉ አስቀድመን የእግዚአብሔርን መንግስትና ጽድቁን

እንድንሻ ያስተምረናል። እንግዲህ በዚህ አግባብና ከእግዚአብሔር ቅደም ተከተል አኳያ “ፕሮቶን”

የሆነው ጉዳይ መንግስቱና ጽድቁ ናቸው። ለሰው ልጅ እግዚአብሔር ዋና የሚለው፣ አንደኛ

የሚለው፣ ቀዳሚ የሚለው፣ በልጫ ያለው የሚለው ጉዳይ ወደ መንግስቱ የመግባትና ጽድቁን

የመካፈል ጉዳይ ነው። እግዚአብሔርም ለሰው ካለው ሃሳብ አንጻር የመንግስቱና የጽድቁ ጉዳይ

ቀዳሚ ነው። መግስቱና ጽድቁን ቅስቀድመን ሌላውን ማስከተል ነው መለኮታዊው ቅደም-ተከተል።

ነገር ግን ሌላውን አስቀድመን መንግስቱንና ጽድቁን ተከታይ ካደረግን በመለኮት ስሌት ኪሳራ ነው።

ትርፍ የለውም። እግዚአብሔርን ያስቀደመውን ስናስቀድም በእርሱ ሃሳብ ውስጥ እንገባለን።

የግዚአብሔር መንግስትትና የእግዚአብሔር ጽድቅ ተወራራሽ ናቸው። ወደ እግዚአብሔር

መንግስት መግባት የምንችለው የርሱን ጽድቅ ከያዝን ነው። በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል የተገለጸው

የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው። ስለዚህም ቃሉ “አሁን ግን በሕግና በነቢያት የተመሰከረለት

የእግዚአብሔር ጽድቅ ያለ ሕግ ተገልጦአል፥ እርሱም፥ ለሚያምኑ ሁሉ የሆነ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ

በማመን የሚገኘው የእግዚአብሔር ጽድቅ ነው” (ሮሜ 3:21-22)። ወደ እግዚአብሔር መንግስት

ለመግባት በክርስቶስ ኢየሱስ ማመንና የእግዚአብሔርን ጽድቅ ማግኘት አለብን። ለዚህም ነው

የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለችና ንስሃ ግቡ ተብሎ የተሰበከው። ወደ መንግስቱ የምንገባው

በንስሃ ታጥበን እግዚአብሔር የሚቀበለውን ጽድቅ ስንይዝ ነው። በክርስቶስ ስናምን የእግዚአብሔር

የራሱ ጽድቅ የኛ ጽድቅ ሆኖ ይቆጠርልናል። ስለዚህ ጌታ በቃሉ ያስተማረን ከሁሉ በፊት አስቀድመን

ደህንነትን እንድንሻ ነው። እርግጥ ነው ሰው አለሙን ሁሉ አትርፎ ነፍሱን ግን ቢያጎድል ምን

ይጠቅመዋል? ስለ ነፍሱስ ዋጋ ምን ይሰጣል? ሕይወታችን ከመብል፣ ከልብስ፣ ከንዋይ፣ ከዝና፣ እና

ከስልጣን ይበልጣል። አስቀድመን ወደ እግዚአብሔር መንግስት የሚያስገባንን ጽድቅ መፈለግ

አለብን። ያን ካደረግን ሌላው የሚያስፈልገን ሁሉ ይጨመርልናል። አሜን!


Recent Posts
Archive
Search By Tags
No tags yet.
Follow Us
  • Facebook Basic Square
  • Twitter Basic Square
  • Google+ Basic Square
spotify-badge-button-listen-wh-BG.png
apple-podcasts-logo.jpg
Google-Podcasts-Badge.jpg
RadioPublicc.png
breaker.png
pocketcasts3.png
Anchor-Podcast-Logo.png

 

5850 N. Elston Avenue 

Chicago, Il 60646

10:00 AM TO 12:00 PM SUNDAY

7:00PM TO 9:00PM FRIDAY

  • Facebook Social Icon
  • Twitter Social Icon
  • Google+ Social Icon
  • YouTube Social  Icon
bottom of page